Back to Top
የተውሒድ ክፍሎችን ከተጨማሪ ማብራሪያና ምሳሌዎች ጋር ቢዘረዝሩልን?

ጥያቄ(8): የተውሒድ ክፍሎችን ከተጨማሪ ማብራሪያና ምሳሌዎች ጋር ቢዘረዝሩልን?
መልስ:

አላህን አስመልክቶ የተጠቀሱ የተውሒድ ክፍሎች በሙሉ ጥቅላዊ የተውሒድ ትርጓሜ ውስጥ ይካተታሉ። እርሱም አላህን ሱብሃነሁ ወተዓላ በሚነጠልበት እና ከፍጥረታቱ በሚለይበት ነገር ሁሉ ለይቶ ማምለክ ማለት ነው።የተውሒድ ክፍሎች ሦስት ሲሆኑ እነርሱም፦

አንደኛው ተውሒዱ ሩቡቢያህ ይባላል። እርሱም አላህን በመፍጠር በማስተዳደር እና በማስተናበር መነጠል ማለት ነው። አላህ ብቻውን ፈጣሪ ነው ከርሱ ውጭ ሌላ ፈጣሪ የለምና።

አላህ እንዲህ ይላል፦

“ከአላህ ሌላ ፈጣሪ አለን? ከሰማይና ከምድርም ሲሳይን የሚሰጣችሁ አለን?” [ፋጢር:3]
የከሃዲያን አማልክቶች ውድቅ መሆናቸውን ሲገልፅ አላህ እንዲህ ይላል፦ “የሚፈጥር እንደማይፈጥር ነውን? አታስተውሉምን?” [አን ነሕል:17]

አላህ ብቻውን ፈጣሪ ነው ሁሉንም ነገር ከፈጠረ በኋላ በልኩና በመጠን አደረገው። መፍጠር ሲባል የእርሱ እና የፍጥረታት ድርጊቶችን ያካተተ ነው። ለዚህም ሲባል በቀደር ማመን የተሟላ የሚሆነው አላህ የባሮችንም ድርጊት የፈጠረ መሆኑ ስናምንና ስናረጋግጥ ብቻ ነው። አላህ እንዳለው፦

«አላህ እናንተንም የምትሠሩትንም የፈጠረ ሲኾን፡፡» [አሷፋት:96]

ይህም የሆነበት ምክንያት የሰው ልጅ ድርጊቱ ከባህሪያቱ የሚመደብ ሲሆን የሰው ልጅ ደግሞ በአላህ ችሎታ የተፈጠረ ነው።አንዳችን ነገር የሚፈጥር ባህሪውንም ፈጣሪ እርሱ ነውና። ሌላኛው ደግሞ አንድ ሰው የሚፈፅመው ድርጊት በተሟላ ችሎታና በቁርጠኛ ውሳኔ ነው። ፍላጎትና ችሎታ ደግሞ ሁለቱም ፍጡር ናቸው። ቀጣዩ የቁርኣን አንቀፅ እንደሚጠቁመው መፍጠር ከአላህ ውጭ ላለ አካል ፀድቆ ሊመጣ ይችላል፦

“ከፈጣሪዎችም (ከቀራጮችም) ሁሉ በላጭ የሆነው አላህ ላቀ፡፡” [አልሙእሚኑን:14]

  እንዲሁም የአላህ መልክተኛ ሰዓሊያንን አስመልክቶ እንዲህ ብለዋል፦

“የፈጠራቹት ነገር ላይ ህይወት ዝሩበት ይባላሉ።”

ለዚህም መመሳሰል ምላሽ የሚሆነው ከአላህ ውጭ ያለ አካል መፍጠሩ እንደ አላህ አይሆንም የሚል ይሆናል። ምክንያቱም ሰዓሊ ያልነበረን ነገር ወደ መኖር አይቀይርምና። የሞተንም ሕያው ማድረግ ይሳነዋል። ከአላህ ውጭ ያለ አካል የተወሰኑ ለውጦችን ሲያስገኝ  ፈጠረ የሚል ትርጉም ሊሰጠው ይችላል። ከአንድ ገፅታ ወደ ሌላ ገፅታ መለወጥ ግን ይህ የአላህ ድርጊት ወይም ፍጥረት ብቻ ነው ሊሆን የሚችለው። ለምሳሌ አንድ ፎቶ የሚያነሳ ሰው ፎቶ ቢያነሳ ምንም የፈጠረው ነገር የለም። እዚህ ላይ የመጨረሻ ሊባል የሚችለው ነገር ቢኖር አንድን ነገር ወደ ሌላ ነገር ለወጠ ነው የሚባለው። እንደዚሁም በጭቃ የወፍ ቅርፅን አሊያም ቢሰራ ፤ የግመል ቅርፅ በቀለማት ነጭ ሉክን ቢያቀልም ቀለማት ሁሉ የአላህ ፍጥረት ናቸው ነጩም ወረቀት እንዲሁ። "ሰዎች ይፈጥራሉ" እና "አላህ ይፈጥራል" ሲባል በመሃላቸው ያለው ልዩነት ይህ ነው። ስለዚህም አላህ ፍጥረታት በማይጋሩትመልኩ  ለየት ያለ መፍጠር ለርሱ አለው ማለት ነው።

ሁለተኛው ከተውሒድ አሩቡቢያ አካል ከሆነው መካከል አንዱ አላህን በሹመት መነጠል ነው። አላህ ብቻውን አስተዳዳሪ ንጉስ ነው። አላህ እንዳለው፦

“ያ ንግሥና በእጁ የኾነው አምላክ ችሮታው በዛ፡፡ እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡” [አልሙልክ 1]

እንዲህም ይላል፦ «የነገሩ ሁሉ ግዛት በእጁ የኾነ እርሱ የሚጠብቅ በእርሱ ላይ የማይጠበቅ (ጥበቃ የማይሻ) ማን ነው? የምታውቁ እንደኾናችሁ (መልሱልኝ)» በላቸው፡፡” (ሙዕሚኑን :88) ልቅ የሆነና ያልተገደበ ንግስናና ስልጣን ያለው ለአላህ ብቻ ነው። ከአላህ ውጭ ያለ አካል ንጉስ ነው ሲባል አንፃራዊ ንግስና ነው። አላህ በቁርኣን ውስጥ ፍጡር ለሆነ አካል ንግስና አፅድቆለት እናገኘዋለን። አላህ እንዲህ ይላል፦

“ወይም መክፈቻዎቹን የበላይ በሆናቹበት ቤት (ብትበሉ) ኀጢአት የለባችሁም፡፡” [አኑር:61]

እንዲህም ይላል፦

“በሚስቶቻቸው ወይም እጆቻቸው በያዟቸው (ባሪያዎች) ላይ ሲቀር፡፡” [አልሙእሚኑን :6]

እነዚህና ሌሎች ሹመትን ከአላህ ውጭ መኖሩን የሚገልፁ አንቀፆች ይኖራሉ ነገርግን ይህ ንግስና እና ሹመት እንደ አላህ አይደለም። ምክንያቱም ሹመቱ ጎደሎ እና የተገደበ ነው። ለምሳሌ ዘይድ የሚባለው ግለሰብ የተሾመበት ቤት ዐምር የሚባለው ግለሰብ አያስተዳድረውም (አይሾምበትም)። በተጨማሪም ንብረቱን ያለ ገደበ እንደፈለገ ማባከን አይፈቀድለትም። አላህ በሚወደው ነገር ላይ እንጂ በሌላ ነገር ላይ ማዋል አይፈቀድለትም። ለዚህም ሲባል የአላህ መልክተኛ ገንዘብን ያለ አግባብ ማባከንን ከልክለዋል። አላህ እንዲህ ይላል።

“ቂሎችንም ያችን አላህ ለእናንተ መተዳደሪያ ያደረጋትን ገንዘቦቻችውን (የያዛችሁላቸውን) አትስጡዋቸው፡፡” [አኒሳእ:5]

የሰው ልጅ ሹመቱና ስልጣኑ ያልተሟላ እና የተገደበ መሆኑን ይህ አንቀፅ ይጠቁማል። የአላህ ሹመት ግን ፍፁም ከዚህ የተለየ ነው። የእርሱ ሹመት ሁሉንም የሚያካትትና የሚያጠቃልል ስልጣን ነው። ለርሱ ሹመት ገደብ የለውም። ያሻውን የሚሰራ ከሚሰራውም ነገር ማንም ጠያቂ የሌለው ሀያል የሆነ ጌታ ነው። ሌላኛው የሩቡቢያ ማዕዘንና አካል ደግሞ አላህ በማስተናበር የተነጠለ ጌታ መሆኑን ማመን ነው። አላህ ሱብሓነሁ ወተዓላ ፍጥረታትን፤ ሰማያትና ምድርን ለብቻው ያስተናብራል። አላህ እንዳለው፦

“ንቁ! መፍጠርና ማዘዝ የእርሱ ብቻ ነው፡፡ የዓለማት ጌታ አላህ (ክብሩ) ላቀ፡፡” [አል አእራፍ፡54]

ይኸኛው ማስተናበር ሁሉንም ያጠቃለለ የማስተናበር አይነት ነው። በሚያስተናብረው ነገር ላይ ከልካይና ተቃዋሚ አካል የለውም። አንዳንድ ፍጡሮች ንብረታቸውን ባሪያቸውን፤ ሰራተኛቸውን እና የመሳሰለውን ሊያስተዳድሩ ይችሉ ይሆናል ነገር ግን ይህ ውስንና የተገደበ ማስተዳደር ነው። ከዚህም ማብራሪያ በመነሳት ተውሒዱ ሩቡቢያ አላህን በፍጥረት ዓለሙ በሹመት እና በማስተናበር መነጠል ነው ብንል አልተሳሳትንም። ይህ ነው የተውሒድ አሩቡቢያ ፅንሰ ሐሳብ።

ሁለተኛው የተውሒድ ክፍል ደግሞ ፦ ተውሒድ ኡሉሂያ ነው። ትርጉሙም አላህን በአምልኮት ነጥሎ ማምለክ ማለት ነው። የሰው ልጅ ከአላህ ውጭ ያለ አካልን ልክ እንደ አላህ ሊያመልከውና ወደ እርሱ ሊቃረብ አይፈቀድለትም። ይኸኛው የተውሒድ ክፍል የመካ ሙሽሪኮች የጠመሙበትና መንገድ የሳቱበት የተውሒድ አይነት ሲሆን መልክተኛው በዚህ የተነሳ ተጋድለዋቸዋል። ሴቶቻቸውንና ዝርዮቻቸው ሊማረኩ ንብረቶቸውንና ግዛቶቻቸውንም  ሀላል ሊያደርጉ የቻሉበት ሚስጥር ይኸው ነው። መልዕክተኞች በሙሉ የተላኩበት ተልእኮ፤ከሰማይ መፅሐፍት የተወረዱበት ዓላማ። ተውሒድ አሩቡቢያ እና ተውሒዱ አስማኢ ወሲፋት የእርሱ አካሎችና መሰሎቹ ጋር ጎን ለጎን ቢጠቀሱም ዋነኛው ግን ተውሒዱ አልኡሉሂያ ነበር። ነግር ግን መልዕክተኞች ከወገኖቻቸው ጋር የሚጋፈጡበትና ከባድ ነቀፌታና ተቃውሞ የሚገጥማቸው በዚህ ተውሒድ ክፍል ላይ ነበር። ይህ የተውሒድ ክፍል ተውሒዱ አልኡሉሂያህ የሚባል ሲሆን መልዕክቱም የሰው ልጅ አካል ቅርብ መላኢካም ሆነ ነቢይና ረሱልነት ማዕረግ ያላቸው አካል፤ ወሊይም ሆነ ፃድቅ እንዲሁም ሌሎች ከአላህ ውጭ ላለ ለማንኛውም ፍጥረታት ከአምልኮ ቅንጣት ታክልም ቢሆን አሳልፎ መስጠት አይፈቀድለትም። በዚህ የተውሒድ ክፍል ላይ ክፍተት ኖሮበት በተውሒድ ሩቡቢያና አስማኡ ወሲፋት ላይ ምንም ችግር ባይኖርበትም እንኳ አካል እርሱ ሙሽሪክና ካፊር ይባላል። ምክንያቱም አምልኮ ከአላህ ውጭ ላለ አካል ለማንም አይገባምና። እንበልና ከሰዎች መካከል አንድ ሰው በአላህ ፈጣሪነት፤አስተናባሪነት እና የሚገቡትን ስሞችና ባህሪያቶችን በሚገባው አረጋግጦ ቢያምን ነግር ግን ከአላህ ጋር ከአላህ ውጭ ያሉ አካላትን የሚያመልክ ከሆነ በሩቡቢያና በአስማኡ ወሲፋት ማመኑ ብቻ ምንም ፋይዳ የለውም። ሩቡቢያና አስማኡ ወሲፋት ሙሉ ለሙሉ ተቀብሎ ነገር ግን ቀብር ዘንድ ሄዶ የሞተን አካል የሚያመልክ አሊያም ለሙታን ስለትን የሚሳል ሰው ቢኖር ይህ ግለሰብ ሙሽሪክና ካፊር ነው ። እሳትም ውስጥ ዘውታሪ ይሆናል። አላህ እንዳለው፦

“እነሆ!  በአላህ የሚያጋራ ሰው አላህ በርሱ ላይ ገነትን በእርግጥ እርም አደረገ፡፡ መኖሪያውም እሳት ናት፡፡ ለበዳዮችም ምንም ረዳቶች የሏቸውም፡፡” [አልማኢዳ:72]

ቁርኣን በሚገባ ያነበበ ሰው እንደሚረዳው መልክተኛው ዘመቻ የከፈቱባቸው፤ ደማቸውና ንብረታቸውን ሐላል ያደረጉባቸው፤ልጆቻቸውን፤ ሚስቶቻቸውን ፤ግዛቶቻቸውንና መሬቶቻቸውን የማረኩባቸው ሙሽሪኮች አላህ ፈጣሪና ጌታ መሆኑን ምንም ሳይጠራጠሩ ያጸድቁ ነበር። ነገር ግን ከአላህ ጋር ሌሎችን አማልክቶችን አብረው በማምለካቸው የተነሳ ደማቸውና ንብረታቸው ሐላል የተደረገባቸው ሙሽሪኮች ሆነዋል።

ሦስተኛው የተውሒድ ክፍል ደግሞ ተውሒዱ አል አስማኢ ወሲፋት ይባላል።  አላህን በስሞቹና በባህሪያቱ ብቸኛ መሆኑን ማመን ሲሆን አላህ እና መልዕክተኛው ያጸደቁትን ስሞችና መገለጫዎች ያለ ተሕሪፍ ትርጉም ሳይዛባ፤ ያለ ተዕጢል (ትርጉም አልባ ሳያደርጉ)፤ ያለ ተክዪፍ (ሁናቴው ሳይጠቀስ)፤ እና ያለ “ተምሲል” (አምሳያ ሳይደረግለት) በማጽደቅ ማመን ማለት ነው። ስለሆነም አላህ  እራሱን በሰየመበት ስያሜዎች እና እራሱን በገለፀበት መገለጫዎች በሐቂቃው ያለ “መጃዝ” ማመን ግዴታ ነው። ታዲያ ይህ መታመን ያለበት ያለ እንዴታ እና ከፍጥረታ ጋር ሳያመሳስሉ መሆን አለበት።

ይህ የተውሒድ ክፍል ከእኛ ጋር ወደ አንድ ቂብላ ዞረው የሚሰግዱ እራሳቸውን ወደ እስልምና ሀይማኖት የሚያስጠጉ በርካታ ጭፍራዎች በተለያየ መልኩ ጥመት ላይ የወደቁበት አጀንዳ ነው። ከነዚህም መካከል ነፍይ እና ተንዚህ ውድቅ ማድረግ ላይ ከልክ ያለፈ መንገድን በመከተላቸው ከኢስላም መውጣት ደረጃ አድርሷቸዋል። ከሙስሊም ጭፍሮች መካከል መካከለኛ አካሄድን የተጓዘ አለ። ከነርሱም መካከል ለአህሉ ሱና ቅርብ የሚባሉ አንጃዎችም አሉ። ነገር ግን ሰለፎች በዚህ የተውሒድ ክፍል ያላቸው አቋም አላህ እራሱን በሰየመበትና እራሱን በገለፀበት ባህሪያት በሐቂቃው ያለ ተሕሪፍ ፤ተዕጢል፤ተክዪፍ እና ያለ ተምሲል መሰየም ነው።

ለምሳሌ፦ አላህ እራሱን ከሰየመባቸው ስሞች መካከል “አል ሐዩ አል ቀዩም” የሚለው ይገኝበታል። ስለዚህም “አል ሐዩ አል ቀዩም” የሚለው ስም ከአላህ ስሞች መካከል አንዱ መሆኑን አምነን መቀበል ይኖርብናል። በተጨማሪም ይህ ስም በውስጡ ያካተተውን መገለጫ ባህሪ ማመን ይኖርብናል። ይህ ስም በውስጡ አቅፎ የያዘው ባህሪም ምሉዕ ሕይወት ማለትም ባለመኖር ያልተቀደመና መጥፋት(መሞት) የማይጠጋው ህይወት ነው። አላህ እራሱን ሰሚዕ እና ዓሊም ብሎ ሰይሟል።ስለሆነም አላህ ሰሚዕ ”የሚሰማ” የሚለው ስምና መስማት የሚለው መገለጫ ባህሪ እንዳለው ማመን ግዴታ ነው። እርሱም ይህ ስምና ባህሪ በሚያስፈርደው መልኩ “ሐከም” ፈራጅ ነው። ያለ መስሚያ ይሰማል ወይም የሚሰሙ ነገሮች ሳይደርስባቸው ይሰማል የሚባለው ፍልስፍና ተቀባይነት የለውም። በዚህ ምሳሌ መሰረት ሌሎችን እያመሳሰልክ እመን(ተገንዘብ)።

ሌላኛው ምሳሌ ፦ አላህ እንዲህ ይላል ፦

“አይሁዶችም «የአላህ እጅ የታሰረች ናት» አሉ፡፡ እጆቻቸው ይታሰሩ ባሉትም ነገር ይረገሙ፡፡ አይደለም (የአላህ) እጆቹ የተዘረጉ ናቸው፡፡ እንደሚሻ ይለግሳል፡፡” [አልማኢዳ:64]

 እዚህ ቦታ ላይ፦”አይደለም (የአላህ) እጆቹ የተዘረጉ ናቸው፡፡” ይላል። አላህ ሁለት የተዘረጉ እጆች እንዳሉት አረጋገጠ። ይህም ማለት ስጦታው እጅግ ሰፊ የሆነ ማለት ነው። ስለዚህም አላህ ጸጋዎችን በማደልና በመስጠት ላይ ዝርግ የሆኑ ሁለት እጆች እንዳሉ ማመን ግድ ይሆንብናል። ነገር ግን እነዚህ ሁለት እጆች በልባችንም ይሁን በአዕምሯችን እንዲሁም በአንደበታችን “ከይፊያ” ማነፃፀር ወይም ከፍጥረታት እጆች ጋር ለማመሳሰል ጥረት አለማድረግ ግዴታ ይሆንብናል። ምክንያቱም አላህ ሱብሃነሁ ወተዓላ እንዲህ ብሏልና

“ለርሱ ምንም አምሳያ የለውም፡፡ እርሱም ሰሚውና ተመልካቹ ነው፡፡” [አሽ ሹራ:11]

እንዲህም ይላል፦

«ጌታዬ እርም ያደረገው መጥፎ ሥራዎችን፣ ከርሷ የተገለጸውንና የተደበቀውን ኃጢኣትንም፣ ያላግባብ መበደልንም፣ በርሱም ማስረጃ ያላወረደበትን (ጣዖት) በአላህ ማጋራታችሁን፣ በአላህም ላይ የማታውቁትን መናገራችሁን ብቻ ነው» በላቸው፡፡” [አል አዕራፍ:33]

እንዲህም ይላል፦

“ለአንተም በርሱ ዕውቀት የሌለህን ነገር አትከተል፡፡ መስሚያ፣ ማያም፣ ልብም እነዚህ ሁሉ (ባለቤታቸው) ከእነሱ ተጠያቂ ነውና፡፡” [አል ኢስራእ:36]

እነዚህ ሁለት እጆች ከፍጥረታት እጆች ጋር ያመሳሰለ የአላህን ቃል እንዳስተባበል ይቆጠራል። “ለርሱ ምንም አምሳያ የለውም፡፡ እርሱም ሰሚውና ተመልካቹ ነው፡፡” [አሽ ሹራ:11] በተጨማሪም ይህን አንቀፅ በማመፁ አላህን ወንጅሏል።

አላህ እንዲህ ይላል፦

“ለአላህም አምሳያዎችን አታድርጉ፡፡” [አን ነህል :74] 

“ከይፊያ” ያደረገ ማለትም እጆቹ እንዲህ እንዲያ ናቸው ብሎ የተናገረ በአላህ ላይ የማያቀውን ተናግሯል። ዕውቀት የሌለው በሆነ ነገር ላይም ተከታይ ሆኗል።

 

 




Share

ወቅታዊ