Back to Top
አላህ ባወረደው ሸሪዓ አለመፍረድ ሲባል ምን ማለት ነው?

ጥያቄ(30): አላህ ባወረደው ሸሪዓ አለመፍረድ ሲባል ምን ማለት ነው?
መልስ:

አላህ ባወረደው ሸሪዓ አለመፍረድ በሁለት ይከፈላል፦

አንደኛው ክፍል፦ አላህ ያወረደውን ሸሪዓ በማስወገድ ሌላ ጣዖታዊ ህግ በቦታው መቀየር ።

ይህ ማለት ሰዎች ላይ ሲፈርድ ሸሪዓን ሙሉ ለሙሉ አስወግዶ በርሱ ፈንታ ሌላ የሰው ሰራሽ ህግ ማፅደቅ ማለት ነው። ይህ ድርጊት የአላህን ሸሪዓ በሰው ሰራሽ ህግ መቀየር ለመሆኑ ምንም ጥርጥር የለውም። ይህ ደግሞ ከኢስላም የሚያስወጣ ኩፍርም ነው። ይህን የሚያደርግ ግለሰብ እራሱን ልክ እንደ ፈጣሪ አድርጓል። ምክንያቱም አላህ ያልፈቀደውን ህግ ለሰዎች ደንግጓልና። እንዲያውም አላህ ያወረደውን ህግ የሚፃረር ህግን አፅድቋል። በሰዎች መካከል ለሚፈጠሩ አለመግባባቶች እራሱን ፈራጅ አድርጎ ሹሟል። አላህ ደግሞ ይህን ድርጊት ከርሱ ጋር ማጋራት መሆኑን እንዲህ ሲል በቁርኣኑ ሰይሞታል፦

“ከሃይማኖት አላህ በእርሱ ያልፈቀደውን ለእነርሱ የደነገጉ ተጋሪዎች ለእነርሱ አልሏቸውን?” [አሹራ:21]

ሁለተኛው ክፍል ፦ የህጎች የበላይ ስልጣን በአላህ ህግጋት መመራት ሆኖ ሳለ ማለትም ሸሪዓው ባለበት የህግ ሁሉ የበላይ ይሆንና ነገር ግን ከነዚህ ህግጋት ተቃራኒ በሆነ መልኩ አንድ መሪ መጥቶ አላህ ባላወረደው ህግ ቢፈርድ ወይም ቢዳኝ ይህንን ሰው አስመልክቶ ሦስት ሁኔታዎች አሉ።

አንደኛው ሁኔታ፦ ሸሪዓውን በሚቃረን መልኩ ሲፈርድ ይህ ተግባሩ በሸሪዓ ከመፍረድ ይበልጣል ወይም ይበልጥ ለሰዎች የሚጠቅመውና የሚበጀው ይህ ነው አሊያም አላህ ካወረደው ህግጋት ጋር ተመሳሳይ ነው አሊያም አላህ ባወረደው ሸሪዓ አለመፍረድ ይቻላል የሚል እምነት ካለው ይህ ተግባር ኩፍር ነው እንላለለን። በዚህም የተነሳ ፈራጁ ወይም መሪው ከኢስላም ይወጣል። ምክንያቱም በአላህ ህግጋት መዳኘት አልወደምና። በተጨማሪም አላህ ያወረደውን ሸሪዓ ሰዎች መካከል መፍርድ ሲኖርበት ይህን ባለማድረጉ ካፊር ይሆናል።

ሁለተኛው ሁኔታ፦ የአላህ ህግ ከሁሉም ህግጋት በላጭና ለሰው ልጆች እጅግ ጠቃሚ ነው በማለት በልቡ አምኖ ነገር ግን አላህ ካወረደው ውጭ የሚፈርድ ፤በዚህም ተግባሩ ወንጀልን እንደሰራ በውስጡ ፀፀት አደረበት  ነገር ግን እንዲፈርድ ያነሳሳው በተከሳሽና በሱ መካከል ጠብና ጥላቻ በመኖሩ ሳቢያ በርሱ ላይ በግፍና በበደል መፍረድ ቢፈልግ፤ አላህ ካወረደው ውጭ የሚፈርደው ሸርዓውን ጠልቶ ወይም በሌላ ህግ (ሸሪዓውን) ለመቀየር ፈልጎ ሳይሆን፤ ተከሳሽን ለመጉዳት ብሎ አላህ ካወረደው ውጭ ህግ ቢፈርድ፤ እዚህ ላይ ፈራጁን(ዳኛውን፣መሪውን) ካፊር ነው አንልም ነገር ግን በዳይ ግፈኛ ነው እንላለን።

ሦስተኛው ደግሞ ፡የአላህ ህግ ከሁሉም ህግጋት በላጭና ለሰው ልጆች እጅግ ጠቃሚ ነው በሚል በልቡ አምኖ ነገር ግን አላህ ካወረደው ውጭ የሚፈርድ ፤በዚህም ተግባሩ ወንጀል የሰራ ስሜት በውስጡ ካደረ ነገርግን እንዲፈርድ ያነሳሳው በነፍሱ ውስጥ ካለ ዝንባሌና መጥፎ ስሜት በመነሳት ለእርሱ ወይም ለሚፈረድለት አካል ጥቅም ሲል አላህ ካወረደው ውጭ የፈረደ እንደሆነ ይህ ተግባር ፊስቅ(አመፅ) እና ከአላህ ትዕዛዝ መውጣት ነው እንላለን። እነዚህ ሦስት የቁርኣን አንቀፆች ከላይ ባሳላፍናቸው ሦስት ሁኔታዎች ለእያንዳንዱ ላይ እናሳርፋቸዋለን።

“አላህም ባወረደው ነገር ያልፈረደ ሰው እነዚያ ከሓዲዎቹ እነርሱ ናቸው፡፡” [አል ማኢዳ:44]

ይህን አንዳኛው ሁኔታ ላይ ስናሳርፈው።

“አላህም ባወረደው ነገር የማይፈርድ ሰው፤ እነዚያ በደለኞቹ እነርሱ ናቸው፡፡”[አል ማኢዳ:45]

ይህን ደግሞ ሁለተኛው ሁኔታ ላይ እናሳርፈዋለን።

“አላህም ባወረደው የማይፈርድ ሰው እነዚያ አመጸኞች እነርሱ ናቸው፡፡” [አል ማኢዳ:47]

ይህንን ደግሞ ሦስተኛው ሁኔታ ላይ እናሳርፈዋለን።

 ይህ ጉዳይ በዘመናችን  እጅግ አደገኛ ከሚባሉ ርዕሶች አንዱ ነው። ምክንያቱም ከሰዎች መካከል ከሙስሊም ውጭ ያሉ ሀገራት የሚደነግጓቸው ህግጋት ላይ በጣም የሚደነቅ እና ልቡ በጣም የሚመሰጥ አለ። ምናልባትም ከመመሰጡና ከመደነቁ የተነሳ ከአላህና ከመልክተኛው ህግጋት የሰው ሰራሽ ህግጋትን የሚያስቀድምም አይጠፋም።

 የአላህና የመልክተኛው ህግጋት እስከ ቂያማ እንደሚቀጥልና እንደሚዘወትር አያውቅም። ምክንያቱ የአላህ መልክተኛ እስከቂያማ ለሚመጡ ሰዎች በሙሉ የተላኩ ነብይ ናቸው። ስለዚህም እስከ እለተ ቂያማ ድረስ ለሰዎች የሚጠቅምና የሚበጅ ነገር ቢሆን እንጂ መልክተኛው ህግን አያፀድቁም። በነቢዩ ዘመን ህግጋቶቹ ይፋ ሆነው ከተደነገጉ ህግግጋት በበለጠ መልኩ አላህ ካወረደው ውጭ ያሉ ህግጋት ለዘመናችና ለሰዎች እጅግ ጠቃሚ ነው ብሎ የተሳሳተ አመለካከት ወይም የሚሞግት ካለ በግልፅ ጥመት ላይ ወድቋል። ስለዚህም ወደ አላህ ተውበት ማድርግ፤ወደ ጤናማ አመልካከት ሊመለስና ቆም ብሎ ስለ ጉዳዩ ሊያስብና ሊያስተውል ይገባል።




Share

ወቅታዊ